አዲስ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ተሾሙ
አዲሷ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ ጽዮን ተክሉ
ተሿሚዋ የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ የነበሩት ወ/ሮ ጽዮን ተክሉ ናቸው
ኢዛ (ዓርብ ሚያዝያ ፲፮ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም. April 24, 2020)፦ ወይዘሮ ጽዮን ተክሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ኾነው መሾማቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።
ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ፤ ወይዘሮ ጽዮን ተክሉ የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ ኾነው ስለመሾማቸው በሚኒስቴሩ የመረጃ ገጽ ላይ አስፍሯል።
በመረጃው መሠረት ወይዘሮ ጽዮን ወደዚህ ሹመት ከመምጣታቸው ቀደም ብሎ የሣይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ኾነው ማገልገላቸውን ይጠቅሳል።
አዲሷ ሚኒስትር ዴኤታ ሹመቱ የተሠጣቸው ከመጋቢት 28 ቀን 2012 ዓ.ም. ጀምሮ መኾኑ ታውቋል። ሹመታቸውን ግን መሥሪያ ቤቱ ያስታወቀው በዛሬው ዕለት፣ ዓርብ ሚያዝያ 16 ቀን 2012 ዓ.ም. ነው። (ኢዛ)



