ባንኮች የባለቤትነት ጥያቄ ያልቀረበበትን ገንዘብ ለብሔራዊ ባንክ አስገቡ ተባሉ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ሕንፃ
ከ18ቱ ባንኮች ድንጋጌው የሚመለከታቸው አሥሩን ብቻ ነው
ኢዛ (እሁድ መስከረም ፲ ቀን ፳፻፲፫ ዓ.ም. September 20, 2020)፦ በሁሉም የአገሪቱ ንግድ ባንኮች ውስጥ በደንበኞቻቸው ተከፍተው ለ15 እና ከዚያ በላይ ዓመታት የባለቤትነት ጥያቄ ሳይቀርብባቸው የቆዩ ተከፋይ ሒሳቦችን፣ ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ እንዲያስገቡ የሚደነግግ ሕግ መውጣቱ ተገለጸ።
የይገባኛል ጥያቄ ያልቀረበበትን ይህንን ገንዘብ ለብሔራዊ ባንክ ካስረከቡ በኋላ፣ በዚህ ሀብት ላይ የሕግ ተጠያቂነት እንደማይቀርብባቸው ይህንን ለማስፈጸም የወጣው መመሪያ ያመለክታል ተብሏል። ይህንን መመሪያ ለማስፈጸምም ባንኮች ማከናወን አለባቸው የተባሉ ድንጋጌዎች በዚሁ መመሪያ ውስጥ ተካትተዋል።
በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ ሁለት የመንግሥትና 16 የግል (በድምሩ 18) ባንኮች እየተንቀሳቀሱ ሲሆን፤ ከ15 ዓመታት በላይ ጥያቄ ያልቀረበባቸው የተከፈቱ ሒሳብ ቁጥሮች ሊገኙ የሚችሉት ከ15 ዓመታት በላይ ላሉት ባንኮች ይኾናል። ከ16ቱ የግል ባንኮች አሥሩ የሚኾኑት ከ15 ዓመት በላይ ዕድሜ ያላቸው ናቸው። (ኢዛ)