ምናለበት?! (ጌታቸው አበራ)
ምናለበት?!
(ለአምባገነኖችና ለግብረ-አበሮቻቸው)
ከጌታቸው አበራ (This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. )
የህዝብ ራዕይ ባታመክኑ፣
ያገር ተስፋ ባታተኑ፣
ያያችሁትን ፍጡር ሁላ - እንደ እብድ ውሻ ባትለክፉ፣
የትውልድን ውብ አበባ - በጭካኔ ባትቀጥፉ፣
ያድባር ቆሌ ባትገፉ፣ የጡር እንባ ባታተርፉ፣
ጣፋጭ ሲሳይ ማር ወለላ - በሬት መራር ባትለውሱ፣
ምናለበትኢ?! ቀኑ አክትሞ - ከመንበሩ ብትነሱ፣
በሥልጣን ጥም ባትሰክሩ፣
ካይጥ ጉድጓድ - የቆቅ ኑሮ ባትኖሩ፣
መውጫ መግቢያው ባይጠባችሁ - ጥላችሁን ባትፈሩ፣
እኩይ ድርጊት ተደራርቦ - ሰው ፊት መቅረብ ባታፍሩ፣
አራጅ፣ ውራጅ ... አምባገነን - የሰቆቃ የጭካኔ ...፣
የዲያቢሎስ ቁራጭ ቁንጮ - ሠይጣን፣ አውሬ፣ አረመኔ፣ ...
ተብላችሁ ተንቃችሁ - የውርደት ሥም ባትለብሱ፣
ምናለበት! ለክብራችሁ - ላገር ክብር ብትሳሱ!!
ልጆቻችሁ ያልታደሉት፣
ፍርሃት ታቅፈው የሚኖሩት፣
አንገት መድፋት፣ መሸማቀቅ - ሽብር፣ ሥጋት፣ ... ሳይገባቸው፣
ባደባባይ ቢራመዱ - ልበ-ሙሉ ኩሩ ሆነው ... ፣
ህዝበብ ሲራብ፣ ሀገር ሲወድም - ጥሪ ማሸሻ በያለበት፣
ላትበሉት ለዝንተ-ዓለም - ላትኖሩ ምዕተ-ዓመት፣
መኖር ከቶ እንዲያኮራ - በንጽኅና በነፃነት፣
ከማንዴላ፣ ከኦባማ፣ ... - ብትማሩ ምናለበት?!
የብዙኃን ምክር፣ ቁጣ፣ ... - የህዝብ ድምፅ ባትንቁ፣
ልቦናውን ቢሰጣችሁ - ከእንቅልፋችሁ ብትነቁ፣
ብልጽግና፣ ሠላም፣ ፍቅር፣ ... - ፍትህ፣ ጤና፣ ... እንዲያብቡ፣
ሰብዓዊነት እንዲሰፍኢኢ - እፎይ ብሎ ሊኖር ህዝቡ፣
እንዲከበበር ክቡር ድምፁ - ሳያሰልስ ሲወተውት፣
ሳትተብቱ ብትሰሙ - ቢያምርባችሁ ምናለበት?!
አልያ ግን ካልገባችሁ - የህዝብ እንባ ያገር ብሶት፣
አሁን ደርሶ ምናለበት?! - ቢጠርጋችሁ አንድ መዓት!!
ጌታቸው አበራ
ኅዳር 2001 ዓ.ም. (ኖቨምበር 2008)