“ሽፈራው - ሞሪንጋ”ን የሚመለከት አዲስ መጽሐፍ ወጣ
ጋዜጠኛ፣ ገጣሚና ደራሲ አበራ ለማ “ሽፈራው - ሞሪንጋ” የተሰኘ አዲስ መጽሐፍ አሣተመ። ሞሪንጋ ወይም ባገራችን “ሽፈራው” እያልን በስፋት የምንጠራው ዕጽ፣ እጅግ እውቅናን አግኝቶ የኖረው በእስያ ውስጥ ነው። ሕንዶች ኦሊፌራ የተሰኘው ዝርያ ባለጸጎች በመሆናችው በብዙ መልኩ ሲጠቀሙበት ኖረዋል። ዛሬ ኦሊፌራ የተሰኘው ዝርያ፣ በሰሜንና ደቡብ አሜሪካ፣ በካሪቢያን ደሴቶች፣ በአፍሪካና በኦሴኒያ ውስጥ በብዛት እየለማና እየተስፋፋ ነው።
አገራችን በሽፈራው ወይም በሞሪንጋ ዕጽ ሀብት ባለቤትነት ከሚጠቀሱ አገሮች አንዷ ናት። ቢያንስ በአራት የተለያዩ የሽፈራው ዝርያዎች ባለቤትነት ተመዝግባለች። “ያፍሪካ ሞሪንጋ” ወይም “የጎመን ዛፍ” እየተባለ የሚጠራው የእስቴኖፔታላ ዝርያ በብዛት የሚገኘው አንድም ባገራችን ነው። ራቫይ፣ ሩስፖሊያናና ሎንጊቱባ የተባሉትም የሞሪንጋ ዝርያዎች ባገራችን የሚገኙ ናቸው። አለመታደል ሆኖ ግን ሕዝባችን እነዚህን ዕጾች በመጠቀሙ ኋላ ቀር ነው። ይህም ችግር ሊፈጠር የቻለው ሕዝቡ ስለ ዕጹ ምንነትና ጥቅም እምብዛም ሳያውቅ መኖሩ ነው።
ባገራችን ስለሽፈራው ምንነትንና ጥቅም ቀዳሚውን እውቅና የሰጠው የኮንሶ ብሔረሰብ ነው። ኮንሶዎች ለረዥም ዓመታት ምግባቸውም አብነታቸውም አድርገው ተጠቅመውበታል። ከጊዜ በኋላ በዚሁ ባገራችን የሽፈራው ዕጽ ዙሪያ፣ አንዳንድ ያገራችንም ሆኑ የውጭ አገር ተመራማሪዎች ሰፊ የምርምርና የስርጸት ተግባርን አከናውነዋል።
አገራችንን በመሳሰሉ የተመጣጠነ የምግብ እጥረት ባለባቸው አገሮች ውስጥ፣ ሽፈራው የድሃው ሕዝብ አለኝታ ነው። ይህ ከ300 በሽታዎች በላይ የመፈወስ ኃይል ያለው ዕጽ፣ “ታምረኛው ዛፍ” የሚል የማዕረግ ስም ማግኘቱም ያለምክንያት አይደለም።
ይህ መጽሐፍ የተዘጋጀው፣ ሕዝቡ የዕጹን እያንዳንዱን ጥቅም ሁሉ አውቆ ከቀዳሚዎቹ ተጠቃሚ የሌላው ክፍለ ዓለም ሕዝብ ጎራ እንዲሰለፉ ለማበረታታት ነው። ከሽፈራው ምንነት ጀምሮ እስከ አተካከሉና ለገበያ አቀራረቡ ጭምር፣ በመጽሐፉ ውስጥ ተካቷል። መጽሐፉ እንደመመሪያ የሚያገለግል በመሆኑ፣ እያንዳንዱ ቤተሰብ እንዲጠቀምበት ኾኖ የተዘጋጀ ነው።
መጽሐፉን አሳታሚና አከፋፋይ
አሳታሚ፡- ማንኩሳ አሣታሚ ድርጅት፣
አከፋፋይ፡- ዓይናለም የመጻሕፍት መደብር፣
ስልክ ቁ. +251 911 62 49 10
አዲስ አባባ