እያንጓለለ - የምርጫ ጭውውት (ዳግማዊ ዳዊት)
እያንጓለለ (የምርጫ ጭውውት)
ዳግማዊ ዳዊት This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.
እያንጓለለ …
ያ ገብስማ ዶሮ - ዘንድሮስ ምን አለ?
ሊቀ መኳስ ቆመ - አራት ኪሎ ላይ
ትናንት መለስ መለስ …
ዛሬም መለስ መለስ …
ነገም መለስ መለስ - መለስ መለስ ባይ።
ሀገር አሳደጉ
ሠላም አወረዱ
ይህን አድርገዋል - ስሙ ያልሰማችሁ
ተገቢ ነውና - በሙሉ ድምፃችሁ
ለዘንድሮው ምርጫ - እነርሱን ባትመርጡ
ትዝብት ነው እንጅ - ምንም አታመጡ።
ኩኩሉ አለ ዶሮ
የምን ምርጫ ነው ዘንድሮ
ውጤቱን ያወቅነው ገና ዱሮ
መለስ ሊመረጥ ዞሮ ዞሮ
እያንጓለለ …
ያ ገብስማ ዶሮ - ዘንድሮስ ምን አለ?
መሪው ሊቀ መኳስ - አጭር ሰው መላጣ
“ላሌ ላሌ” እያለ - ይኸውና መጣ።
“ቂ ... ቂ …
ልደቱ ልደቱ - እያሉ ሲያለቅሱ
እነኃይሉም መጡ - ከእኔ ሊቋደሱ”
ኩኩሉ አለ ዶሮ
ማን ነው የሚገደል ዘንድሮ
ማን ነው አስገዳይ ዘንድሮ
እያንጓለለ …
ያ ገብስማ ዶሮ - ዘንድሮስ ምን አለ?
ያዝ ልደቱ …
አውቄ ነው እንጅ ድሮም ስግደረደር
እኔስ ለአድዋው ሰው - አሽከር ሆኘ ልደር
እንደምን ነው ስሜን - ወገብ ለወገቡ
እንደምን ነው ትግራይ - ወገብ ለወገቡ
የእነአዜብዬ ሀገር - የእነአይጠገቡ
አላማጣ ውዬ - መልሸ አላማጣ
ሽህ ሰው ይተላለቅ - እናንተን ከማጣ
እኔስ በመለስ ላይ - ክፉም አላመጣ።
ኩኩሉ አለ ዶሮ
ምን ተደግሶልናል ዘንድሮ
እያንጓለለ …
ያ ገብስማ ዶሮ - ዘንድሮስ ምን አለ?
ያዝ መለስ …
ብለነው ብለነው - የተውነውን ነገር
አምና ኃይሉ ሰምቶ - ታንቆ ሊሞት ነበር
ዘንድሮ መምጣቱ - መስማማቱ ላይቀር
ልደቱን መውቀሱ - ተገቢም አልነበር።
ሀገራችን ትግራይ - ወንዛችን ተከዜ
ማነው እምቢ የሚል - ምርጫ ባልን ጊዜ።
እያንጓለለ …
ያ ገብስማ ዶሮ - ዘንድሮስ ምን አለ?
ኩኩሉ አለ ዶሮ
ኃይሉስ ምን አለ ዘንድሮ
በእስር በእንግልቴ - ሁሉ እማስብሽ
እኔም ልመጣ ነው ፓርላማ እንዴት ነሽ?
ኤልያስ የሚሉት - የሻዕቢያ ምላስ
መለስ ጠላት ብሎ - ህዝብን ሲቀሰቅስ
እኔም ወንድነቴ - ነሸጥ አድርጎኝ
ፓርላማ መግባቴ - ውርደት ነው አልኩኝ
ያ ክፉ ባለጌ - አሳሳተኝና
ባለፈው ባልመጣ - ባላይሽ ታችሃምና
ዘንድሮ ቁርጥ ነው - እንገናኛለን
እንዲህ ተለያይተን - መች እንቀራለን
መልክ ሰጠኝ እንጅ - ሲሉ እሰማ ነበር
ሙያ ከልደቱ - ይኸው ጀመርኩ መማር።
እኔም ላሞግሰው - ልነሳ አደግድጌ
የአድዋው ሰውዬ - ባይሆን አብሮ አደጌ
አክብሮ ጥሪዬን - እጀን ሲጨብጠኝ
ከእራሴ ጀምሮ - ወገቤን ነዘረኝ።
ደጋፊ አስፈልጎኝ - በጋሪ ስገፋ
መለስን ስጨብጥ - በሽታዬ ጠፋ።
ይኸው መፎከሬ - “መለስ ይውረድ” ቀርቶ
ሠላም ሠላም ሆኗል - የዘንድሮው ሞቶ።
እኔ ፍራሽ ሆኘ - ልደቱ ትራስ
እንጠብቃለን - አልጋህ እንዳይፈርስ።
እያንጓለለ …
ያ ገብስማ ዶሮ - ዘንድሮስ ምን አለ?
ኩኩሉ አለ ዶሮ
በየነስ ምን አለ ዘንድሮ
ዓመት አስር ዓመት - የደነስኩብሽ
አንች ዉቧ ቆንጆ - ፓርላማ እንዴት ነሽ
ህዝቡ ቢቃወመኝ - አትግባ ቢለኝም
እመኝኝ ፓርላማ - ከአንች አልለያይም።
ዘጠና ሰባትን - ጠፍቶ እሚገድብ
ቅንጅት ተፈጥሮ - ወጣና ከህዝብ
ለጥቂት ተረፍኩኝ - ዱላ ከሚመዝ
ዳግመኛ እንዳይመጣ - ያን መሳይ መዘዝ።
ወያኔ ስትዳር - ጎጆ ስትቀልስ
ያን ጊዜ ጀምሮ - እስካሁን ድረስ
ታማኝ ተቃዋሚ - ሆኘ ለመለስ
መልካም ተብሎ ለእኔ - ህዝብም ተዘናግቶ
ያልፈኛል ሁልጊዜ - እንዳላዬኝ አይቶ።
ኩኩሉ አለ ዶሮ
ምን መዓት ይመጣል ዘንድሮ
እያንጓለለ …
ያ ገብስማ ዶሮ - ዘንድሮስ ምን አለ?
ያዝ ኃይሉ …
አድዋ ላይ ሆኖ - መለስ ቢደነፋ
ብርሃኑ ነጋ - ሀገር ጥሎ ጠፋ
ድሮም በእጀ - ያልኩት መስፍንን አምኘ
ያኔ እርሱን ማመኔም - ፍፁም የዋህ ሆኘ
“በብልቃጥ ተረግዞ - መስታወት ተወልዶ”
ድርጅት መባሉም - ወይ ነዶ ወይ ነዶ
እንግዲህስ በቃኝ - መስፍን የለ ሌላ
ጠቃሚ ላይሆኑ - የኋላ የኋላ
ፓርላማው ሰፊ ነው - ቧ ያለው መንገዱ
ሥነ ምግባር ብቻ መፈረም ነው ኮዱ።
ቀብቸ አሽሞንሙኘ - ከላይ ባረግሽ
አምባገነን ብለሽ - ስሜን አጠፋሽ
በገዛ ምላሷ - በገዛ አንደበቷ
ቃሊቲ ገብታለች - ከዘላለም ቤቷ
አትሳቂ እያልኳት - ባህር ማዶ ስቃ
አመጣችው እስሩን - ነቅንቃ ነቅንቃ።
ኩኩሉ አለ ዶሮ
በችግር ላይ ችግር ሆኖ የእኛ ኑሮ
እያንጓለለ …
ያ ገብስማ ዶሮ - ዘንድሮስ ምን አለ?
ያዝ ብርሃኑ …
ስሙልኝ ይኸን ሰው - እዩት ስም ሲያጠፋ
ምርጫ ውሸት ነው ብል - አለኝ ጥሎ ጠፋ
እኔስ ያከበርኩህ - በሽምግልናህ ነው
አመራር ሲመጣ- ጉድክን ሳስተውለው
አምባገነንነት - ፍፁም መለያህ ነው
እነ መለስ ዜና - ሰይጣን መርቋቸው
ተቃዋሚ ጀባ - ብለው በጫታቸው
አንገዋለለና - ልደቱን ሰጣቸው
አንገዋለለና - በየነን ሰጣቸው
አንተን በምራቂ - ይኸው ጨመራቸው
እያንጓለለ …
ያ ገብስማ ዶሮ - ዘንድሮስ ምን አለ?
ያዥ ብርቱካን …
ዓለም ዓለም … ዓለም ዓለምዬ
እሽሩሩ ስቃይ - ውረድ ከጀርባዬ
ደብተራው የማነ - አረጋሽ እህቴ
አብረው የሚኖሩ - ቤታቸው ከቤቴ
የእግዜር ፈቃድ ሆኖ - ቢሰማ ፀሎቴ
ለፍች ያብቃችሁ - ከዓላማችሁ ግብ
አምላክ ያውርድና - የሠላም ድባብ።
ዛሬ በመልዓኩ - በገብርኤል በበዓሉ
ወዲ መለስ ዜና - መሸረብ ጀመረ አሉ
ኃይሉ መላጣ ላይ - ሽሩባ ጎንጉኖ
“እኔን እኔን ሥራኝ” ይላል ልደት አብሮ
ፀጉር እንዲህ ይሠራል - ከክዳን ጀምሮ።
ተወኝ አላልኩም ወይ - ይህን ዓመልህን
ልክ እንደልደቱ - አንተም መክዳትህን
ልደቱስ ቢያንስ እንኳን - ይሂድ ይመለሳል
ምርጫ መጣ ሲሉት - መለስን ይወቅሳል።
እያንጓለለ …
ያ ገብስማ ዶሮ - ዘንድሮስ ምን አለ?
* * * * * * * * *
ኩኩሉ አለ ዶሮ
አራት ኪሎ አስመራን ምን ይላል ዘንድሮ
ያዝ መለስ …
ከሰማዩ በላይ - ያለኸው ሰማይ
ወዲ አፎም በጤናው - ዘግቶኝ ቀረ ወይ
ደግሞ በዚህ ምርጫ ያደናቅፍ ወይ?
የቀይ ዳማ ረጅም - ጎራዴ ታጣቂ
ልግደልህ እያለኝ - እኔ እርሱን ናፋቂ
እያንጓለለ …
ያ ገብስማ ዶሮ - ዘንድሮስ ምን አለ?
ኩኩሉ አለ ዶሮ
ኢሳያስ ምን ይላል ዘንድሮ
ልቤ አብጦ ጀግኘ - አንበሳ ነኝ ስል
ጦር አዘመትክና - አደረከኝ ድል
አስራ ሁለት ሌሊት - አስራ ሁለት ቀን
ከትግራይ ተነስትህ - ልትይዝ አስመራን
ጉዴ ፈልቶ ነበር - ክሊንተን ባይኖር
ያስጎራሃል አሉ - በየአምስት ዓመት
ደም የለመደ እጅህ - ሲሻ መስዋዕት
ሲሉ ሰምታ ሆኖ - ሆነና ነገሩ
ምዕራብ ያለው ሁሉ - ይመስልሃል ጥሩ።
ምርጫ ምርጫ - ብለህ ብትፈጥር ግርግር
እኔ ጌታህ ሆኘ - ካልሆንከኝ አሽከር
ውጊያ መቀስቀሱ - ምንጊዜም አይቀር።
እያንጓለለ …
ያ ገብስማ ዶሮ - ዘንድሮስ ምን አለ?
ያዝ መለስ ...
ጠያቂው ቢያስጨንቀኝ - ስለኤርትራ ሁኔታ
አልወዳትም አልኳቸው - እንዲያገኙ ፋታ።
ቁርጡማ ሲመጣ - አስመራ ልትያዝ
የኔ ተግባር ነበር - እነስየን ማዘዝ
አልጀርስ ሳገኝህ - ውል ልትፈራርም
አልነበረምና - እኔ ያልኩኝ ጥምጥም
ይናፍቃል ለካስ - እንደዚያ ወንድም።
እያንጓለለ …
ያ ገብስማ ዶሮ - ዘንድሮስ ምን አለ?
ያዝ ስዬ …
ተወኝ አላልኩም ወይ - ይህን አመልህን
ጫት እንዳዬ ጀዝባ - አስመራን መዞርክን
ጫትን ያዬ ቃሚስ - ቅሞ ይመለሳል
የአንተ ሁኔታ ግን - ግራ ነው እሚያጋባን።
እያንጓለለ …
ያ ገብስማ ዶሮ - ዘንድሮስ ምን አለ?
ኩኩሉ አለ ዶሮ
ህዝባችን ምን አለ ዘንድሮ
የሚመጣው ምርጫ - ምኞታችሁ መክኖ
የፍትህ አካላት - ፕሬስ ነፃ ሆኖ
ገለልተኛ ሆኖ - መከላከያችን
ገለልተኛ ሆኖ - የምርጫ ቦርዳችን
በነፃ እንዲሰማ - እንደ ህዝብ ድምፃችን
በዘር በኃይማኖት - መጋጨት ትታችሁ
ኤርትራና ትግራይ - አማራ ኦሮሞ ማለቱን ትታችሁ
አብዮት - አብዮት ማለት አቁማችሁ
ሁላችንን በእኩል - ሕጉ እንዲመዝነን
የሥልጣኑ ምንጮች - እኛ ህዝቡ እንሁን።
ዳግማዊ ዳዊት This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.
ጥር 2002 ዓ.ም.



